• Call Us
  • +251465512106

ሀሽያ/Hashiya/

ሀሽያ /Hashiya/

ይህ በወላይታ በሥራ የመረዳዳት ባህል ከ2 እስከ 5 የሚደርሱ በአንድ መንደር እና በአንድ አካባቢ የሚኖሩና እርስ በርስ የሚተዋወቁ አርሶ አደሮችም ሆኑ ወጣቶች ከማለዳው 12 ሰዓት ጀምረው ቢያንስ እስከ ቀኑ ስድስት ሰዓት/ግማሽ/ ቀን ድረስ የእርሻ ሥራን በጋራ ተጋግዘው የሚሠሩበት በሥራ የመረዳዳት ባህል ነው፡፡ ሀሽያ ተብሎ በሚጠራው በወላይታ በሥራ የመረዳዳት ባህል ውስጥ ጠንከር ያለ መተዳደሪያ ደንብ /Norm/ የለም፡፡ ነገር ግን በሀሽያ የሚረዳዱ አርሶ አደሮች ጧት ከመኝታ እንደተነሱ እርስ በርስ ተጠራርተው የሀሽያ ሥራ ወዳለበት አርሶ አደር ማሣ በመሄድ ከቀኑ እስከ ስድስት ሰዓት ድረስ ሥራ በመሥራት ይለያያሉ፡፡ እነዚህ አርሶ አደሮች እስከ ግማሽ ቀን ከሰሩ በኋላ ወደ ገበያ፣ ወደ ለቅሶ አለበለዚያም ወደ ራሳቸው ግል ሥራ ሊሰማሩ ይችላሉ፡፡

አንዳንድ ጊዜ በሀሽያ በመረዳዳት ሥራ የሚሰሩ ግለሰቦች እስከ 3 ሰዓት፣ ወይንም 4 ሰዓት አንዳንዴ ደግሞ እስከ ግማሽ ቀን ድረስ ሊተጋገዙ ይችላሉ፡፡ ሀሽያ በሥራ የመረዳዳት ባህል እንደግለሰቦች በጎ ፈቃድና ውሳኔ መሠረት የሚከናወን ነው፡፡ በሀሽያ በሥራ የመረዳዳት ባህል በአንድነት እየሠሩ ካሉ ግለሰቦች መካከል አንዱ በተረኛው ሥራ ላይ ካልተገኘ ቅጣት አይጣልበትም፡፡ ምክንያቱም በቀረው ግለሰሰብ ላይ የሚጣል ቅጣት ባይኖርም ያልተሳተፈውን ተራው ሲደርስበት ግለሰቡ ሳይመጣ ይቀራል፡፡ በሀሽያ የመረዳዳት ስርዓት ሁሉም አባላት ተነጋግረው በተስማሙበት መሠረት ይሠራሉ ማለት ነው፡፡ ሀሽያ በሥራ የመረዳዳት ባህል ውስጥ አባላቱ እስከ ምሣ ሰዓት በሥራ ላይ የማይቆዩ ከሆነ ምሳ አይዘጋጅላቸውም፡፡ ይሁን እንጂ በቁርስ ይቀርብላቸዋል፡፡ ምሳቸውን ግን ወደየቤታቸው ሄደው ይበሉና በዛው ወደግል ሥራቸው ይሄዳሉ፡፡ ቀን ሙሉ በሥራ ላይ የሚውሉ ከሆነ ቁርስም ሆነ ምሣ ይዘጋጅላቸዋል፡፡ በአጠቃላይ ሀሽያ ከፍ ብሎ በተጠቀሱት ሰዎች ቁጥር የሚሠሩት በሙሉ ፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተ ሥራ ባህል ነው፡፡