ሰዎች ከአራዊትና ከተለያዩ አደጋዎች ራሳቸውን ለመጠበቅ የግላቸው የሆነ የተከለለ ቦታ ወይም ማረፊያ ሊኖራቸው ግድ ነው፡፡ ስለሆነም ሰው ከጥንት ዋሻ ውስጥ ኑሮ ከወጣበት ጊዜ ጀምሮ የራሱ ወይም የግሉ የሆነ መጠለያ በመሥራት መኖር እንደጀመረ ይታወቃል፡፡
የወላይታ ብሔርም ለመኖሪያነት አቅሙ የፈቀደውን ዓይነት ጎጆ ቤት በመስራት ይኖራል፡፡ የዚህ ጎጆ ቤት አሰራርም በአራት ዓይነትና ደረጃ ተከፍሎ የሚታይ ይሆናል፡፡
ለሁሉም የጎጆ ቤት ዓይነቶች አይቀሬ የሆኑ ተግባሮች አሉ፡፡ እነርሱም፡-
ሆሆ ሆያ ሆ
ሀያ ማዳ ማድያጎ
ሀያ ማዳ ጦሳው
ትርጓሜው፡- አጋዡ አምላካችን ናና አግዘን… ሆ… ሆ.. እንደ ማለት ነው፡፡ እያሉ በቅብብል እያዜሙ ወደቦታው ይደርሳሉ፡፡ የአቅራቢያው ሴቶችም በሙሉ ወጥተው ከበሮ እየደለቁ እና እልልታውን እያቀለጡ ቀየውን በደስታ ያደምቃሉ፡፡ ወንዶች ወደ በሩ ጋ ሲደርሱ ከላይ የተባለውን ዜማ በመቀየር
“ኬታዋይ ጋኮሆ…
ኬታዋይ እማታይ ጋኮሆ…
ትርጓሜው፡- እንግዳው ደርሶ የለም ወይ ባለቤቱ ደርሶ የለም ወይ? ማለት ነው… እየደጋገሙ እያሉ እያዜሙ በሴቶች እልልታና ከበሮ ድለቃ ታጅቦ ምሶሶው በበር ገብቶ በቀጥታ መስመር አልፎ ይጋደማል፡፡
የምሶሶው ማቆሚያ ጉድጓድ ጥልቀቱ በግምት ሶስት ክንድ ያህል ይሆናል፡፡ ምሶሶው ከጫፍ ወደ ግንዱ ጋ ሶስት ክንድ ያህል ተለክቶ በመሮ ይበሳና በቀዳዳው የ “ምጫፍሌ” የሚባለው መሳቢያ ይሰካለታል፡፡ ሌላው የምሶሶው ጫፍ ተደበልብሎ ይጠረባል፡፡ ከዚያም ተጎትቶ ቀና ይልና ከጫፉ አቅጣጫ ይጋደማል፡፡ ቀጥሎም ጣሪያውን ለማምጣትና ምሶሶው ጫፍ ላ ለመሰካት ምሶሶውን ጎትቶ ያመጣው ሰው ሁሉ ወደዚያው ያቀናል፡፡ “ጦሳ ማዳ.. ሃያ ማዳ.. እያለ በሴቶች ከበሮ ድለቃና እልልታ አጃቢነት በጫፉ ላይ ጣሪያውን ይሰካና ሲመለከቱት የማይቻል የሚመስለውን የተሰበሰበው ደቦ ህብረቱን አጠናክሮ ሆሆ.. ሆያ ሆ.. እያለ ብድግ አድርጎ ያቆመዋል፡፡ የሴቶቹም እልልታ እንደገና ይቀልጣል፡፡
በዚህ መልኩ ምሶሶው እንደቆመ ወራጅ አጠና (ዛሮ ዛፍያ) ከውጭ በኩል ዙሪያው ይተከልለታል፡፡ ከህዝቡ ወይም ደቦ መካከል ሙያተኛ ናቸው የተባሉት ሁለት ወይም አራት ሰዎች ጣሪያው ላይ ይወጡና ወራጅ አጠናውን መሬት ላይ የቆሙ ሰዎች በቆልማማ (Hingettaa) በተሰኘው እንጨት መያዣ እየሳቡላቸው ይዘው በጣሪያው ላይ በማሠር የወራጅ ሥራ ይጠናቀቃል፡፡
በአጠቃላይ የወላይታ ባህላዊ ጎጆ ቤት በውስጥ አወቃቀሩ፣ በስፋት ጥበቱ፣ በዘመን ተሸጋርነቱ፣ ለመሥራት በሚፈጀው ጊዜና ቁሳቁስ ዓይነት በአጠቃላይ በጥርት ደረጃው በአራት ተከፍሎ ይታይ እንጂ የሚያመሳስለው እና ለሁሉም አይቀሬ የሆኑ ነገሮች እንዳሉት መታወቅ አለበት፣ ለምሳሌ የምሶሶ አቋቋም የግድግዳና የቢሮ ወይም መቃን አወቃቀር፣ የጣሪያ ሥራና የውስጥ ክፍፍል ወዘተ… ተጠቃሾች ናቸው፡፡ የአሰራሩ ስልቱ ይለያይ አንጂ አራቱም ዓይነት ቤቶች ተመሳሳይ ደረጃዎችን ያልፋሉ፡፡
ለአራቱም የጎጆ የቤት ዓይነቶች ሥራ ከመጀመሩ አስቀድሞ ዝግጅት ይደረጋል፡፡ ከዝግጅቶቹም መካከል ዋና ዋናዎቹ ምሶሶ፣ ወራጅ፣ ሰንበለጥ፣ ወፍቾ… ወዘተ ቁሳቁሶችን መሰብሰብ የግድ ይሆናል፡፡
ማንኛውም ዓይነት ቤት ሲሰራ ለምሶሶ የሚሆነው ግንድ በቅድሚያ ተጠንቶ ሳይቆረጥ ይቆያል፡፡ ቤቱ ምሶሶ እንዲቆምለት ከተዘጋጀ በኋላ ግን የደቦ (Daguwaa) ህብረት ምሶሶው ቆርጦ ሳይውል ሳይድር ዕለቱኑ እንዲቆም ያደርጋል፡፡ ይኸም የሚሆነው ምሶሶው ከዋለና ካደረ ውሻ ወይም ሌላ ጸያፍ እንስሳ በላዩ ላይ ቢያልፍ ቅስፈት ያመጣ የሚል እምነት ስላለ ነው፡፡ ለምሶሶነት የሚመረጡ የእንጨት ዓይነቶች ዋንዛ (moqqottaa)፣ ዶቅማ (ochchaa)፣ ግራር (odooruwaa)ና ብርብራ (ዛጊያ) ወዘተ ናቸው፡፡
እነዚህ የእንጨት ዓይነቶች በጣም ጠንካራ እና በሚሰጥ የማይደፈሩ ናቸው ተብሎ ስለሚታመን ነው፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን ባህር ዛፍም ለምሶሶነት ተስማሚ (shaaga) ተብሎመከበር እንደተጀመረ ይታወቃል፡፡
ከደጃፉ ላይ የጥራጥሬ ማስቀመጫ ጎተራ፣ ከጓሮ ደግሞ በእንሰትና በተለያዩ ተክሎች የታጀበ ውብ የወላይታ ጎጆ ቤት በዚህ መልክ ተሰርቶ ይጠናቀቃል፡፡
ማጠቃለያ
የወላይታ ጎጆ ቤቶች ለመኖሪያ ምቹ ከመሆናቸውም በተጨማሪ ባህሉን ከማጉላትም ከማስተዋወቅም አንጻር ትልቅ ሚና የሚጫወቱ ሆነው ሳለ በአሁኑ ጊዜ በሰዎች አስተሳሰብና ኢኮኖሚያዊ ለውጥ ተጽእኖ በቆርቆሮ ቤቶች አየተተኩና እየጠፉ ስለሆነም በአንዳንድ አከባቢዎች የሚገኙ ባህላዊ ቤቶችን የብሔሩ ተወላጆችም ሆነ ለባህሉ ተቆርቋር የሆኑ ግለሰቦች ትኩረት ሰጥተው ለታሪክ እንዲቆዩ ለማድረግ የራሳቸውን አስተዋጽኦ ቢያደርጉ መልካም ነው እንላለን፡
Copyrights 2019. . All Rights Reserved.
Developed by SNNPRS-SITB & SNNPRS-wza