Zayiya/ዛይያ/ወንፈል/
ዛይያ የሚባለው ከ5 እስከ 10 የሚደርሱ ሰዎች አንዳቸው ከአንዳቸው ጋር በመሆን በሥራ የሚረዳዳበት ስርዓት ነው፡፡ እነዚህ ግለሰቦች ተራ በተራ የግላቸውን ሥራ በጋራ ሰርተው የሚበለጽጉበት ህብረት ነው፡፡ ዛይያ በወላይታ ብሔር ዘንድ የተለመደና እስካሁንም ያለ በሥራ የመረዳዳት ባህላዊ ስርዓት ሲሆን ከአንድ ሰው አቅም በላይ የሆነውንና ስፋት ያለውን ሥራ በአጭር ጊዜ ውስጥ ለማጠናቀቅ በሥራ የሚረዳዱ ሰዎች ተሰባስበው ተረኛው አርሶ አደር ያቀደውን ሥራ ሰርተው የሚነሱበት ስርዓት ነው፡፡ የዛይያ ስርዓት እንደሀሽያ ስርዓት በአንድ መንደር የሚኖሩ እና በአንድ ሀሳብ ሊስማሙ የሚችሉ ግለሰቦች ተስማምተውና ተግባብተው ከዕለተ ሰንበት ውጪ ባሉት ቀናት ከጧቱ 12 ሰዓት አከባቢ በመነሳት ሥራው ወዳለበት አርሶ አደር ማሣ ሄደው በሥራ ተጋግዘው የሚለያዩበት ነው፡፡
ለዛይያ የሚመጡ መንደርተኞች ለሥራ ሲመጡ ለሥራው አስፈላጊ የሆኑ ቁሳቁሶችን ይዘው ነው የሚመጡት፡፡ የዛይያ አባላት ለሥራ ሲመጡ ተረኛ የሆነው አርሶ አደር ቁርስና ምሣ በራሱ ቤት አዘጋጅቶ የሚጠብቅ ሲሆን ምንም ዓይነት ለየት ያለ መጠጥ አይዘጋጅም፡፡ ተረኛው አርሶ አደር ቁርስም ሆነ ምሣ ቤት ያፈራውን በማዘጋጀት ለሚሰሩ ሰዎች ያቀርባል እንጂ ለየት ያለ ዝግጅት አይኖርም፡፡ ቁርስንም ሆነ ምሳ የሚያዘጋጁት የቤቱ ሰዎች ናቸው እንጂ ከጎራቤት ለእገዛ የሚመጣ ሰው አይኖርም፡፡ ምናልባት ምግብ የሚታዘጋጀው የአርሶ አደሩ ባለቤት ለመውለድ የተቃረበችና አራስ ከሆነች ከጎራቤት አንድ ወይም ሁለት ሴቶች ሊያግዟት ይችላል፡፡ ዛይያ በሥራ የመረዳዳት ባህላዊ ስርዓት ላይ ከእርሻ ሥራ ውጪ የተለያዩ ሥራዎችን ማከናወን ይቻላል፡፡ ለምሳሌ ትልቅ የሆነውን የወላይታ ጎጆ ቤት ለመሥራት የሚፈልግ ግለሰብ በዛይያ የቤቱን መሠረት በመደልደል ማዘጋጀት ይችላል፡፡ ሌሎች የእርከን ሥራዎችም ሊሰሩ ይችላሉ፡፡ በእርሻ ጊዜ ዘር በዛይያ አማካይነት ሊዘራ ይችላል፡፡ የኩትኳቶና የአረም ሥራዎችም በዛይያ ሊከናወኑ ይችላሉ፡፡
ዛይያ በሥራ የመረዳዳት ባህላዊ ስርዓት አባላት በአንድ ቀን በሁለት ሰዎች ማሳ ሊወጡ ይችላሉ፡፡ ምክንያቱም በአዝመራው ወቅት የዘር ጊዜ እንዳያልፍ ለማድረግ ከጧት እስከ ቀኑ 6 ሰዓት ድረስ በአንድ ሰው ማሣ ዘር ዘርተው ከቆዩ በኋላ ከሰዓት ደግሞ በሁለተኛው አርሶ አደር ማሳ ዘር እየዘሩ ይውላሉ፡፡ በወላይታ ብሔር አባባል ‹‹ Badhdheesay sheeshshawu uttidaashin aadhdhees›› ይባላል፡፡ ይህም ከአዝመራ ወቅት ለሽንት እንኳን መውጣት አያስፈልግም እንደማለት ነው፡፡ የአዝመራ ወቅት እንዳያልፍ ለማድረግ በዛይያ የተደራጁ አርሶ አደሮች በአንድ ቀን በሁለት ሰዎች ማሣ ዘር ዘርተው ሊውሉ ይችላሉ፡፡
Copyrights 2019. . All Rights Reserved.
Developed by SNNPRS-SITB & SNNPRS-wza